ወደ ይዘቱ ዝለል
ቀጥታ ዝማኔ
ሀሁኒውስ

ግልጽና የታመነ ዜና

የውጭ ሀገር ዜጎች በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን አሰራር የሚወስን አዲስ መመሪያ ወጣ

ምንጭ፦ TIKVAH Ethiopia

·

አጋራXFacebookTelegramLinkedIn
የውጭ ሀገር ዜጎች በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን አሰራር የሚወስን አዲስ መመሪያ ወጣ
የውጭ ሀገር ዜጎች በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን አሰራር የሚወስን አዲስ መመሪያ ወጣ

በመመሪያው ድንጋጌ መሰረት የውጭ ሃገር ዜጎች በመንግስት ቀጥተኛ ድጎማ የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም)  ባለቤት መሆን አይችሉም።

የከተማና መሰረተ-ልማት ሚኒስቴር የውጭ ሀገር ዜጎች በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን ዝርዝር ሁኔታ የሚወስን "መመሪያ ቁጥር 1147/2018" አውጥቷል።

መመሪያው የወጣው የውጭ ሀገር ዜጎች የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን አግባብ ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ ቁጥር 1388/2017 በጥቅሉ የተቀመጡ ጉዳዮችን በመለየት፣ የመኖሪያ ቤት ባለቤት ለመሆን የሚፈልጉ የውጭ ሀገር ዜጎች ማሟላት የሚገባቸውን ቅድመ ሁኔታዎች፣ ገደቦች እና ክልከላዎች በዝርዝር ለመደንገግ ነው።

የውጭ አገር ዜጋ ማለት ትውልደ ኢትዮጵያዊ የሆነ የውጭ ዜጋን ሳይጨምር ኢትዮጵያዊ ዜግነት የሌለው ወይም የሌላ አገር ዜግነት ያለው ማንኛውም ሰው ማለት መሆኑን የመመሪያው ትርጓሜ ያስረዳል።

በመመሪያው መሰረት፣ ማንኛውም የውጭ ሀገር ዜጋ የመኖሪያ ቤት ባለቤት ለመሆን የሚያስችል ፈቃድ ከሚኒስቴሩ ለማግኘት የሚከተሉትን መስፈርቶች ማሟላት አለበት፡-

• የጸና ፓስፖርት እና የጉዞ ሰነድ ማቅረብ፤

• የጸና የመግቢያ ቪዛ ወይም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖር ከሆነ የጸና ቋሚ የመኖሪያ ፈቃድ፤

• ከሚኖርበት ሀገር የሚሰጥ ከወንጀል ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ ማስረጃ፤

• ለቤት ግዥ የሚውል ዝቅተኛ የገንዘብ መጠን በባንክ ገቢ ማድረጉን የሚያሳይ ማስረጃ፤

• የውጭ ባለሀብት ከሆነ ደግሞ በኢንቨስትመንት ውስጥ ቢያንስ 150,000 የአሜሪካ ዶላር ድርሻ ያለው መሆኑን የሚገልጽ የኢንቨስትመንት ፈቃድ እና የጽሁፍ ማረጋገጫ ማቅረብ ይኖርበታል።

መመሪያው እንደ አካባቢው ለቤት ባለቤትነት የሚያስፈልገውና የውጭ ሃገር ዜጋው ማቅረብ የሚጠበቅበት ዝቅተኛ የገንዘብ መጠን በዝርዝር አስቀምጧል።

• በአዲስ አበባ እና በሸገር ከተማ አስተዳደሮች የመኖሪያ ቤት ባለቤት ለመሆን ቢያንስ 150,000 የአሜሪካ ዶላር

• በኦሮሚያ(ሸገርን ሳይጨምር) ፣ አማራ፣ ትግራይ፣ ሲዳማ፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ ደቡብ ኢትዮጵያ፣ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ፣ ሶማሌ፣ ሐረሪ ክልሎች እና ድሬዳዋ አስተዳደር 120,000 የአሜሪካ ዶላር፤

• በአፋር፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ወይም ጋምቤላ ክልሎች ደግሞ ቢያንስ 100,000 የአሜሪካ ዶላር ማቅረብ ይኖርበታል።

በተጨማሪም ማንኛውም የውጭ ሀገር ዜጋ በኢትዮጵያ ውስጥ ሊኖረው የሚችለው ከፍተኛ የቤት ብዛት አንድ ብቻ እንደሆነ ተደንግጓል።

ማንኛውም የውጭ ሀገር ዜጋ ለመኖሪያ ቤት የሚሆን የውጭ ምንዛሬ በመረጠው ባንክ ገቢ ለማድረግ በመጀመሪያ ከሚኒስቴሩ የፈቃድ ደብዳቤ ማግኘት የሚኖርበት ሲሆን ባንኩም የቀረበለትን ምንዛሬ በዕለቱ ተመን ወደ ብር በመቀየር በዜጋው ስም በተከፈተ ዝግ የባንክ ሂሳብ ውስጥ ያስቀምጣል።

በዝግ ሂሳብ የተቀመጠው ገንዘብ የሚለቀቀው ግለሰቡ ቤት ሲገዛ ወይም በሊዝ ጨረታ መሬት ሲያገኝ ብቻ ይሆናል ይህም የሚከናወነው ሚኒስቴሩ ገንዘቡ እንዲለቀቅ የሚገልጽ የፈቃድ ደብዳቤ ለባንኩ ሲያቀርብ ባንኩ በአሰራሩ መሰረት ገንዘቡን እንዲለቀቅ ሲያደርግ ነው።

በሽብር ወንጀል፣ በሰው መነገድ፣ በአደገኛ ዕጽ ዝውውር፣ በገንዘብ ማጠብ፣ በከባድ ሙስና፣ በሳይበር ወንጀል እና በሌሎች ከባድ ወንጀሎች የተጠረጠረ ወይም ጥፋተኛ የተባለ ሰው የመኖሪያ ቤት ባለቤት መሆን አይችልም።

በተጨማሪም በመንግስት ቀጥተኛ ድጎማ የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም)፤ ከትርፍ ውጭ ለሆነ ዓላማ በመንግስት ወይም ከህዝብ በተሰበሰበ ገንዘብ የተገነቡ ቤቶች፤ በመንግስት፣ በባለሀብት ወይም በመንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች ድጋፍ የተገነቡ ቤቶች፤ በህብረት ስራ ማህበራት የተገነቡ ቤቶች የውጭ ሀገር ዜጎች በባለቤትነት ሊይዟቸው አይችሉም።

ለባለቤትነት ፈቃድ ለማውጣት 50 የአሜሪካ ዶላር በዕለቱ ምንዛሬ መከፈል እንዳለበት መመሪያው ይደነግጋል።

የሚሰጠው ፈቃድ ለአንድ ዓመት ብቻ የሚያገለግል ሲሆን፣ ግለሰቡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ቤት መግዛት ወይም መስራት ካልቻለና ከአቅም በላይ የሆነ ምክንያት ካጋጠመው ለተጨማሪ አንድ ዓመት ሊታደስለት ይችላል። ፈቃዱን ካልተጠቀመበት ግን ለሚኒስቴሩ መመለስ ይኖርበታል።

የመኖሪያ ቤቱን ላልተፈቀደ ወይም ለህገ-ወጥ ዓላማ የተጠቀመ የውጭ ሃገር ዜጋ ከ1,000 እስከ 3,000፣ ያለ ፈቃድ የመኖሪያ ቤት ባለቤት ሆኖ የተገኘ ከ2,000 እስከ 5,000 ዶላር እንዲሁም ህገ-ወጥ መሆኑን እያወቀ የረዳ ወይም የተባበረ ማንኛውም ሰው ከ30,000 እስከ 50,000 የኢትዮጵያ ብር መቀጮ እንደሚጣልበት መመሪያው ያመለክታል።

ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ነሐሴ 5 ቀን 2018 ዓ/ም

@tikvahethiopia

ተዛማጅ ታሪኮች